የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍ/ቤት የፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት ስልጣን የለውም ተባለ

በጌታቸው ሺፈራው
የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የከፍተኛ ፍርድ ቤት ስልጣኑን አጥቷል ሲል ብይን ሰጥቷል። ጥቅምት 23/2010 በእነ ብርሃኑ ሙሉ እና ነጋ የኔው ክስ መዝገብ ስር ክስ የተመሰረተባቸው ተከሳሾች ወንጀሉን ፈፀሙት የተባለው በአማራ ክልል በመሆኑ በወንጀለኛ ወቅጫ ህግ ስ/ስ/ቁ 99 እና 100 መሰረት ወንጀሉ ተፈፀመበት በተባለው ቦታ ክሱ ሊታይ እንደሚገባ ባቀረቡት የክስ መቃወሚያ ፍርድ ቤቱ የአማራ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ስልጣንን ስላጣ ጉዳዩን ሊያይ አይችልም ሲል በአብላጫ ድምፅ በይኗል።
ፍርድ ቤቱ የክልል ፍርድ ቤቶች የፌደራል ፍርድ ቤት ስልጣን የተሰጣቸው ኢትዮጵያ በአህዳዊ መንግስት ትተዳደር በነበረችበት ወቅት እንደነበር፣ በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ የምትተዳደረው በፌደራል ስርዓት ስለሆነ የስነ ስርዓት ህጉ ተፈፃሚ አይሆንም ሲል በአብላጫ ድምፅ ወስኗል።
ፍርድ ቤቱ በአብላጫ ድምፁ የህገ መንግስቱ አንቀፅ 78 ለክልል ፍርድ ቤቶች የፌደራል ስልጣን የሰጣቸው በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በ2/3ኛ ድምፅ በክልሎች የፌደራል ፍርድ ቤት እስኪቋቋም ብቻ መሆኑን ገልፆአል።
በአዋጅ ቁጥር 322/95 መሰረት በጋምቤላ፣ ቤንሻንጉል፣አፋር፣ ሶማሊና ደቡብ ህዝቦች ክልየፌደራል ፍርድ ቤቶች ስለተቋቋሙ የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት በዚህ ወቅት የፌደራል ፍርድ ቤት ስልጣኑን አጥቷል የሚል ብይን ተሰጥቷል። የችሎቱ የማህል ዳኛ በአምስት ክልሎች የፌደራል ፍርድ ቤት መቋቋሙ የሌሎች ክልሎችን የፌደራል ፍርድ ቤቶች ስልጣን አያስቀርም በማለት የልዩነት ድምፅቸውን አስመዝግበዋል።
የአማራ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት ከሰጠው ብይን በተቃራኒ ለፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የተሰጡ ጉዳዮች እየዳኘ የሚገኝ ሲሆን በአብነትም የኮለኔል ደመቀ ዘውዱን ጨምሮ የ”ሽብር” ክስ የቀረበባቸውን ሌሎች ተከሳሾች ጉዳይ እያየ ይገኛል። በኦነግና ግንቦት ሰባት ክስ ቀርቦባቸው ወንጀሉ ተፈፀመበት በተባለባቸው ክልሎች እንዲታይ ያቀረቡት ተቃውሞ ውድቅ ሲደረግ የቆየ ቢሆንም ተከሳሾችና ጠበቆቻቸው የፍርድ ቤቶቹ ብይን ከህገ መንግስቱ የሚቃረን መሆኑን በመግለፅ ቅሬታቸውን ሲያቀርቡ ቆይተዋል።
የተከሳሾቹ ጠበቃ አቶ አለልኝ ምህረቱ ” ዛሬ የሰማሁት ብይን በባህሪው እንግዳ ነው። የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤትን ስልጣን አጥቷል መባሉ የህግ ባለሙያዎችን ሊያነጋግር የሚችል ጉዳይ ነው” ብለዋል። ጠበቃ አለልኝ በብይኑ ስለማይስማሙም ለሚመለከተው ፍርድ ቤት ይግባኝ ለማቅረብ እንዳሰቡ ገልፀውልኛል።
እነ ብርሃኑ ሙሉ እና እነ ነጋ የኔው በቀረባቸው ክስ ላይ ያቀረቡት ሁሉም መቃወሚያ ውድቅ ተደርጎ አቃቤ ህግ የጠቀሰባቸውን የሰው ምስክር ለመስማት ለህዳር 20/2010 ቀጠሮ ተይዟል። አቶ ነጋ የኔው የወልቃይት ህዝብ አማራ ማንነት ጥያቄ ኮሚቴ አባል እንደነበሩ የ ተገለፀ ሲሆን ጎንደር ከተማ ውስጥ ጥቃት ፈፅማችኋል ተብለው ተከሰዋል።

አቶ አባይ ጸሀዬ ለሕክምና ከሀገር እንዲወጡ ተደርጓል ሲሉ የኢሳት ምንጮች ገለፁ ተባለ

በኢትዮጵያ ውስጥ በሚካሄደው ሌብነት በግንባር ቀደምትነት ሲጠቀሱ የነበሩትና ከሀገር እንዳይወጡ እገዳ ተጥሎባቸው የቆየው አቶ አባይ ጸሀዬ ለሕክምና ከሀገር መውጣታቸውን ምንጮች ለኢሳት ገለጹ።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ራሳቸውን በኮሚቴ ያደራጁ የትግራይ ምሁራንና የሀገር ሽማግሌዎች በሌብነት ላይ የተጀመረው ዘመቻ እንዲቆምና የታሰሩትም እንዲፈቱ መጠየቃቸው ተሰምቷል።

በኢትዮጵያ ውስጥ በሚካሄደው ሌብነት በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀሱት አቶ አባይ ጸሃዬ ናቸው።

ይህን ተከትሎም ከሀገር እንዳይወጡ እገዳ ተጥሎባቸው መቆየቱም የሚታወስ ነው።

ሌቦችን የማደኑ ስራ እየተካሄደ ነው በሚባልበት በአሁኑ ሰአት ደግሞ ራሳቸውን በኮሚቴ ያደራጁ የትግራይ ምሁራንና የሀገር ሽማግሌዎች በሌብነት ላይ የተጀመረው ዘመቻ እንዲቆምና የታሰሩትም እንዲፈቱ በመጠየቅ ላይ መሆናቸውም ተሰምቷል።

እነዚህ በኮሚቴ ተደራጁ የተባሉት የትግራይ ምሁራንና የሀገር ሽማግሌዎች ባሳደሩት ተጽእኖም አቶ አባይ ጸሀዬ ለሕክምና ከሀገር እንዲወጡ ተደርጓል ሲሉ የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል።

ባለትዳርና የልጆች እናት ከሆኑት ወይዘሮ ሳሌም ከበደ ጋር በአንድ ጣራ ስር መኖራቸው የተገለጸው አቶ አባይ ጸሀዬ ወይዘሮ ሳሌም ከበደ ከታሰሩ በኋላ በምርመራ እየወጡ ያሉ የወንጀል ድርጊቶቻቸው እንዲሁም ባለቤታቸውን መታደግ አለመቻላቸው በፈጠረባቸው ውጥረት መታመማቸውን ምንጮች ገልጸዋል።

ራሳቸውን በኮሚቴ ያዋቀሩት የትግራይ ምሁራንና የሀገር ሽማግሌዎች አቶ አባይ ጸሃዬ በሕወሃት ትግል ውስጥ በመሪነት ጭምር የተጫወቱትን ሚና በመዘርዘር እንዳይታሰሩ ሲማጸኑ መቆየታቸውም ተመልክቷል።

ይህ ርምጃ በሕዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ ውስጥ ያለውን ችግር ያባብሳል፣ለጠላትም በር ይከፍታል በሚል የጸረ ሌብነት ዘመቻው እንዲቆም ሲወተውቱ መቆየታቸውም ተሰምቷል።

የታሰሩትም ይቅርታ ጠይቀው በማስጠንቀቂያ እንዲፈቱም ተማጽኖ ማቅረባቸው ታውቋል።–የታሰሩትን ለመፍታት ስለመወሰኑ የታወቀ ነገር ባይኖርም እንኳን።

ሆኖም ክትትል ሲደረግባቸው የነበሩትና ይታሰራሉ ተብለው የሚጠበቁት ባለስልጣናትና ነጋዴዎች የሚደረግባቸው ክትትል መቆሙን እነዚሁ ምንጮች ገልጸዋል።

በሀገሪቱ በሚፈጸመው ሌብነት ፊታውራሪ ተብለው የሚጠቀሱት አቶ አባይ ጸሃዬ ለሕክምና እንዲሄዱ የተፈቀደው በሌብነት ላይ የተጀመረው ዘመቻ በመቆሙና ከትግራይ ሽማግሌዎች ተጽእኖ ጋር በተያያዘ እንደሆነም መረዳት ተችሏል።

አቶ አባይ ጸሃዬ ለህክምና የወጡት ወደ ጀርመን እንደሆነ ቢገለጽም በትክክል ወደየትኛው ሀገርና የህክምና ማዕከል እንደሄዱ ግን ማወቅ አልተቻለም።

በአማራ ክልል ህዝባዊ ተቃውሞ ሊቀሰቀስ እንደሚችል ተጠቆመ

በአማራ ክልል ከወልቃይት ጠገዴ ጉዳይ ጋር ተያይዞ ህዝባዊ ተቃውሞ ሊቀሰቀስ እንደሚችል
ተጠቆመ፡፡ የክልሉን ህዝብ አስተዳድራለሁ ባዩ ብአዴን፣ ከወልቃይት ጋር የተያያዘ መሬት ለትግራይ
አሳልፎ መስጠቱ ብዙዎችን እያስቆጣ ይገኛል፡፡ መረጃዎች እንደጠቆሙት ከሆነ፣ ብአዴን መሬቱን
ለትግራይ ክልል መንግስት ወይም ለህወሓት አሳልፎ መስጠቱ ከተሰማ ወዲህ፣ በአማራ ክልል
ከፍተኛ ቁጭት አጭሯል፡፡ ውሳኔውን የተቃወሙ የአማራ ተወላጆች በማኅበራዊ ሚዲያ
ተቃውሟቸውን በመግለጽ ላይ ይገኛሉ፡፡


ሐሙስ ጳጉሜ 2 ቀን 2009 ህወሓት ከብአዴን ጋር በሰጠጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ‹‹ከዚህ በኋላ
የወልቃይት ጉዳይ አብቅቶለታል፡፡›› በማለት ከድንበር ጉዳይ ጋር ተያይዞ የተነሳው ውዝግብ
መቋጨቱን ገልጸው ነበር፡፡ ምንም ዓይነት ህዝባዊ ውሳኔ ባልተካሔደበት ሁኔታ፣ በህወሓት ትዕዛዝ
ተመርቶ መሬቱን ለትግራይ ክልል አሳልፎ የሰጠው ብአዴን፣ ከክልሉ ተወላጆች ከፍተኛ ተቃውሞ
እየገጠመው እንደሚገኝ ታውቋል፡፡


‹‹ብአዴን የአማራን ህዝብ እያስጠቃ ይገኛል›› ያሉት አስተያየት ሰጪዎች፣ ለራሱ አሽከር መሆኑ
ሳያንሰው ህዝቡንም የህወሓት አሽከር ለማድረግ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል ብለዋል፡፡ ለትግራይ ክልል
ተላልፈው የተሰጡት ጎቤ እና ግጨው የተባሉት የድንበር አዋሳኝ መሬቶች የአማራ ክልል ሀብት
መሆናቸውን የክልሉ ተወላጆች ይናገራሉ፡፡ ሆኖም በብአዴን አማካይነት መሬቱ ለማይመለከተው
ህወሓት ተላልፈው ተሰጥተዋል-ይላሉ ታዛቢዎቹ፡፡ ይህን ህገ ወጥ ድርጊት ለመቃወምም በቅርቡ
ህዝባዊ ተቃውሞ ሊኖር እንደሚችል ከአማራ ክልል የወጡ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡

የብአዴን የሲቪል ደህንነቶች በወታደራዊ ደህንነቶች እንዲተኩ ተደረገ!!

የህወሓት የእጂ ስራ ብአዴን ለይስሙላም ቢሆን በሚቆጣጠራቸው ትልልቅ ከተሞች በተለይ በባህርዳር ፣ በጎንደር ፣ ደብረታቦር እና ፍኖተ ሰላም ከተሞች ተጠሪነታቸው ለወረዳው የደህንነት መዋቅር የሆኑ ደህንነቶች(ጆሮ ጠቢወች ) በየከተሞቹ ስርዓቱ የሚፈልገውን መረጃ እያቀረቡ ባለመሆኑ ፣ በህዕቡ የሚደርሱ ጥቃቶች ከጥቃቱ በፊትም ይሁን ከጥቃቱ በኋላ ምንም አይነት ፍንጭ ባለመገኘቱ ከጥቃቱ ጀርባ ያሉ የነፃነት ሃይሎችን እና ተባባሪ የስርዓቱ አገልጋዩችን ለመያዝ አዳጋች አድርጎታል።

በዚህም የተነሳ ብአዴን እንደድርጂት ተጠሪነቱ ለህወሓት ወያኔ የሆኑ የደህንነት ባለሙያወች እና የባለስልጣናት ጋርዶችን ለመቀየር በህወሓት በተመረጡ ታማኝ የልዩ ሃይል አድማ በታች የመረጃ ክፍሎች እንዲሁም በፌድራል ፖሊስ እና በመከላከያ ውስጥ ሲሰሩ የነበሩ የወታደራዊ ደህንነቶች በሲቪል የደህንነት ስራውን እንዲሰሩ ተመድበዋል። በየአካባቢው የጆሮ ጠቢወች የስርዓቱን አመራሮች ይከሳሉ። “ችግሩ የኛ አይደለም የምናቀርበው መረጃ ያገኘነውን ነው። የደህንነቱ ምስጢር ከላይ ባሉ ሰወች ውጥቷል ” በማለት የእርስ በርስ የመበላላቱን ጉዞ አጋግለውታል።


በተለይ በባህርዳር እና በጎንደር በሲቪል ደህንነት ሲሰሩ የነበሩ የህወሓት/ብአዴን ቅጥረኞች ተይዘው ምርመራ እየተደረገባቸው እንደሆነ ታውቋል። አሁን ላይ በባህርዳር የወታዳራዊ ሰላዩች የሲቪሉን ሰላይ ስራ ሸፍነው ለመስራት እንደተቸገሩ ከልዩ ሃይል አድማ በታኝ የመረጃ ክፍል የነበረ አሁን ሲቪል ደህንነት ውስጥ ያለ የውስጥ አርበኛ አጋልጧል። ብዙ አመት በዚህ ሙያ ውስጥ ወጣቶችን በመመሳሰል ሲያስልፍኑ ሲያስገድሉ የነበሩትን በማስወጣት ሌሎችን ለመተካት የተገደዱት እያንዳንዱ የህወሓት/ብአዴን ባለስልጣንና ትልልቅ ህወሓት ሰራሽ ባለሀብቶች “ለደህንነታችን እየሰጋን ነው ” በሚል የሚያቀርቡት አቤቱታ እየበረከተ በመምጣቱ እንደሆነ ይነገራል።


በሌላ መረጃ
በእብናት በለሳ አካባቢ የሰፈሩ የስርዓቱ ወታደሮች በየ ጊዜው ከቦታ ቦታ በመቀያየራቸው ክፍኛ እያማረሩ እንደሆነ ተሰምቷል። በተለይ በእብናት ወረዳ ወንበሮች ኪዳነ ምህረት ፣ ወፍጮማ በሚባሉ ስፍራወች ** የነፃነት ሃይሎች በስፋት ይንቀሳቀሳሉ ከነሱም በተደጋጋሚ የሚመጣ መልዕክት ይደርሳችኋል ** በሚል በየጊዜው ወደ ተለያየ ስፍራ እየወሰዷቸው እንደሆነ ተሰምቷል። ከሁለት ሳምንት በፊት በወንበሮች ኪዳነምህረት አካባቢ እንዲዘምቱ የተመደቡ ወታደሮች በአንዲት ዛፍ ላይ ተንጠልጥላ የተገኘች ” ስርዓቱን ከድታችሁ ተቀላቀሉን የሚል ጥሪ ” በቃኝ ሃይሉ አዛዡ እጂ ውስጥ መግባት ወዲያውኑ አሰላለፋን እንዲፕውዙ አድርጓቸዋል። ከ2 ሳምንት በፊት ወደ ቤንሻንጉል መንጌ ወረዳ የተቀየረው አሁን በእብናት ወረዳ የሚገኝ የ፲ አለቃ ወታደር እንደሚለው ” አመራሮቹ ተዘባርቆባቸዋል ! በሳምንት ጊዜ ውስጥ ደግሞ ካነሱን ቦታ መደቡን” ይላል።
ወታደሩ አያይዞም ጊዜና ቦታን እንጂ የምንጠብቀው ሁሉም በወገኖቹ ጉዳት ያረረ በአካል እንጂ በሀሳቡ ከአርበኛ ታጋዩች ጋር ነው ብሏል።
የማይቀረው የነፃነት ብርሃን በህወሓት ውድቀት ይበራል !!

የዶክተር ፍቅሩ ማሩ የዛሬ የፍርድ ቤት ውሎ

በጌታቸው ሺፈራው

ዶክተር ፍቅሩ ማሩ በእነ መቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ የክስ መዝገብ 13ኛ ተከሳሽ ናቸው። በአጋጣሚ ለተከሰተውና ሰባራ ሳንቲም ላልወጣበት የቂሊንጦ ቃጠሎ ማስፈፀሚያ በሚሊዮን ብር ወጭ አድርገዋል በሚል ነው የተከሰሱት። ትናንት ነሃሴ 10/2009 ዓም በመዝገቡ ላይ አራት ምስክሮች ቀርበዋል። ከአራቱ ምስክሮች መካከል አንዱ ዶክተር ተስፋዬ ያዕቆብ ይባላሉ። ዶ/ር ተስፋዬ የጥቁር አንበሳ ሀኪም የነበሩና ሰው ገድለው የታሰሩ መሆናቸውን እሳቸው ጋር አንድ ዞን ታስሮ የነበረ ወዳጄ አጫውቶኛል። ዶክተር ተስፋዬ በአተት ሰበብ ከቤተሰብ የሚገባ ምግብ ስለመከልከሉና ሌሎች ጉዳዮች ላይ የአቃቤ ህግ ምስክር ሆነው ቀርበዋል።

ፍረድ ቤቱ:_ ስም?

ዶ/ር ተስፋዬ ያዕቆብ

እድሜ?

60

ስራዎት?

ሀኪም

አድራሻ?

አዲስ አበባ

ክፍለ ከተማ?

አድራሻዬን ለመንገር ፈቃደኛ አይደለሁም።

አቃቤ ህግ: እስኪ የሚያውቁትን ለችሎቱ ያስረዱልን?

መልስ:_ ነሀሴ 26/2008 አንድ ሀኪም ቂሊንጦ ውስጥ አተት ተነስቷል ብሎ አስረዳ። የቤተሰብ ምግብ አንደማይገባ ተነገረን። በጊዜው ሁሉም ታራሚ ቅሬታውን አሰምቷል። ከዛ በሁዋላ ምግብ እንዳይገባ የሚገልፀው ማስታወቂያ ተለጠፈ። ሁላችንም ፈቃደኞች አልነበርንም። የእስር ቤቱን ምግብ የማንበላ ሰዎች አለን። አተት ሊመጣ የሚችለው በተበከለ ምግብ ነው። ከውጭ የተበከለ ምግብ ይመጣል ስለተባለ የተከለከለው ለታራሚው ጥቅም ነው።

እኔ ስለበሽታው ሁኔታ ገለፃ አድርጌያለሁ። በሚዲያ( በማይክራፎን) አስተላልፍ ተብዬ ተናግሬያለሁ። በማስረዳበት ጊዜ ታራሚው አጉረመረመ። እኔ የበሽታውን መነሻና እንዴት መከላከል እንደሚቻል ነው ያስረዳሁት። ነሃሴ 28/2009ዓም ከተቆጠርን በሁዋላ እስር ቤቱ የሚያቀርበውን ቁርስ አንበላም ተባለ።……… ግርግር ተፈጠረ። ከሌላ ዞን የጥይት ድምፅ ተሰማ። እኔ ጋር የነበሩ እስረኞችን ተባራሪ ጥይት እንዳይመታቸው ቤታቸው ውስጥ እንዲቀመጡ እነግራቸው ነበር። ከሌላ ቤት እየመጡ ውጡ ወንድሞቻችን እየሞቱ ነው የሚሉ ነበሩ። አንድ በጥይት የተመታ ሰው ነበር።

በሁዋላ አበበ የሚባል ከጎንደር የመጣ መቶ አለቃ በታኝ ፖሊሶች መጥተዋል፣ ከታራሚዎች ጋር ይገጥማሉ። ችግር ይገጥመናል፣ ታራሚውን ወደ ቤቱ እንዲገባ፣ ፖሊሶችም ወደ ውስጥ እንዳይገቡ እናድርግ አለኝ። እኛም ተስማምተን፣ አረጋግተን እያንዳንዱ ሰው እቃውን ይዞ እንዲወጣ አደረግን። ( ለአቃቤ ህግ ጥያቄዎች የሰጡት መልስ ጠቅለል አድርጌ አቅርቤው ነው)

ዶክተር ፍቅሩ ማሩ ( መስቀለኛ ጥያቄ):_ ከውጭ የሚመጣ ምግብ በጥንቃቄ ስለማይሰራ ነው አተት የሚያመጣው?

ዶ/ር ተስፋዬ:_ የተበከለ ምግብ ነው አተት የሚያመጣው!

ዶ/ር ፍቅሩ: እሱን አውቃለሁ! ከውጭ የሚመጣው ነው የማረሚያ ቤቱ ነው አተት ሊያመጣ የሚችለው?

ዶ/ር ተስፋዬ:_ ከውጭም ከውስጥም ይሁን የተበከለ ከሆነ ነው!

ዶ/ር ፍቅሩ: _ ገብቶኛል! ከቤተሰብ የሚገባው የተከለከለው የተበከለ ስለሆነ ነው?

ዶ/ር ተስፋዬ: ይበከላል ተብሎ ስለሚታብ!

ዶ/ር ፍቅሩ:_ አተት በተበከለ ውሃ ይመጣል ብለዋል። እስር ቤቱ የታሸገ ውሃ ያቀርባል?

ዶ/ር ተስፋዬ:_ አያቀርብም!

ዶ/ር ፍቅሩ:_ ታዲያ የእስር ቤቱ ውሃ አተት አያመጣም?

ዶ/ር ተስፋዬ:_ ይታከማል። በአጋጣሚ ካልተበከለ አያመጣም።

ዶ/ር ፍቅሩ: ያመጣል? አያመጣም?

ዶ/ር ተስፋዬ: ያመጣል ብዬ አልገምትም!

ዶ/ር ፍቅሩ: መግለጫ ሰጥቻለሁ ሲሉ ነበር!

ዶ/ር ተስፋዬ: አዎ!

ዶ/ር ፍቅሩ: ምን ስለሆኑ ነው መግለጫ የሚሰጡት?

ዶ/ር ተስፋዬ: ሀኪም ስለሆንኩ!

ዶ/ር ፍቅሩ: ተቀጥረው ነው?

ዶ/ር ተስፋዬ: እስረኛ ነኝ። የሙያ ግዴታ አለብኝ!

ዶ/ር ፍቅሩ: ማንም ሀኪም ተነስቶ መግለጫ መስጠት ይችላል?

ዶ/ር ተስፋዬ: የማረሚያ ቤቱን ህግ አላውቀውም!

ዶ/ር ፍቅሩ: ነሀሴ 26 መግለጫ ሰጥተዋል ያሏቸው ሀኪም የምን ሀኪም ናቸው?

ዶ/ር ተስፋዬ: ዶ/ር አለሙ ይባላሉ። ሀላፊ ናቸው።

ዶ/ር ፍቅሩ: የምን ሀላፊ? የቂሊንጦ ነው የቃሊቲ?

ዶ/ር ተስፋዬ: የሁሉም መሰለኝ።

ዶ/ር ፍቅሩ: አሁንም ምግብ ከውጭ እየገባ ነው፣ አሁንስ ሊበከል አይችልም?

ዶ/ር ተስፋዬ…………… (መልስ አልሰጡም)

ዶ/ር ፍቅሩ: ከውጭ የሚገባ ምግብ ማረሚያ ቤቱ ከሚያዘጋጀው በላይ የተከለ ነው?

ዶ/ር ተስፋዬ: አይመስለኝም!

ዶ/ር ፍቅሩ: በአተት ተያዙ የተባሉት ሰዎች በምን እንደታመሙ ያውቃሉ?

ዶ/ር ተስፋዬ: ስላላየሁ አተት ነው አይደለም ማለት አልችልም!

አግባው ሰጠኝ: እርስዎ የቂሊንጦን የባንቧ ውሃ ጠጥተው ያውቃሉ?

ዶ/ር ተስፋዬ: ጠጥቼ አላውቅም!

አግባው:_ ታዲያ የተበከለ ይሁን አይሁን በምን አወቁ?

ዶ/ር ተስፋዬ: ውሃ እንዴት ታክሞ ለህዝብ እንደሚደርስ አውቃለሁ።

አግባው: የእስር ቤቱ ይታከም አይታከም ያውቃሉ?

ዶ/ር ተስፋዬ: ሳይታከም ለህዝብ አይደርስም!

አግባው:_ በሚል ነው?

ዶ/ር ተስፋዬ: በሚል ሳይሆን በእርግጠኝነት!

አግባው: የቧንቧውን ውሃ በጨርቅ አጥልለን እንደምንጠጣው አያውቁም?

ዶ/ር ተስፋዬ:_ አላውቅም! ( ለግንዛቤ ያህል:_ ዶ/ር ተስፋዬና አግባው አንድ ቤት ነበሩ)

መቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ : ከቃጠሎው በሁዋላ ያለው ሁኔታ ይበልጥ ለአተት አያጋልጥም?

ዶ/ር ተስፋዬ: ስለ አተት………………

መቶ አለቃ ማስረሻ: ያጋልጣል አያጋልጥም?

ዶ/ር ተስፋዬ: አጭር መልስ መስጠት አልችልም።

መቶ አለቃ ማስረሻ: ምግብ ከተከለከለበት የማረሚያ ቤቱ ሁኔታና ዝዋይ ከነበሩበት ሁኔታ የትኛው ለአተት ያጋልጣል?

ዶ/ር ተስፋዬ: ነው አይደለም የሚለውን ለመመለስ አተት ምንድን ነው የሚለውን……………

ፍርድ ቤቱ: ለተጠየቁት መስቀለኛ ጥያቄ መልስ መመለስ አለብዎት!

ዶ/ር ተስፋዬ: በማብራሪያ ነው መመለስ የምችለው!

መቶ አለቃ ማስረሻ: ዝዋይ የነበሩበት ሁኔታ ለበሽታ አያጋልጥም?

ዶ/ር ተስፋዬ: አያጋልጥም!

መቶ አለቃ ማስረሻ: ዝዋይ እያለን እጃችን ታጥበን ነበር የምንበላው?

ዶ/ር ተስፋዬ : እጃችን ታጠብን አልታጠብን፣ ባክቴሪያው ዝዋይ አልነበረም!

ፍርድ ቤቱ: ጥያቄውን ይመልሱ!

ዶ/ር ተስፋዬ: እኔ እታጠብ ነበር!

መቶ አለቃ ማስረሻ: ባክቴሪያው ዝዋይ መኖር አለመኖሩን በምን አረጋገጡ?

ዶ/ር ተስፋዬ: ቢኖር ሁሉም ይታመም ነበር!

መቶ አለቃ ማስረሻ: እኛ ወደዝዋይ ስንወሰድ ቂሊንጦ የቀሩ እስረኞች ነበሩ አይደል?

ዶ/ር ተስፋዬ: አላየሁም!

መቶ አለቃ ማስረሻ: እርስዎ 60 አመቴ ነው ብለዋል። ከእርስዎ በእድሜ ያነሱ የ20ና 30 አመት የህወሃት አባል ስለሆኑ ዞን አንድ ተለይተው እንደቀሩ አያውቁም?

ዶ/ር ተስፋዬ: አላውቅም!

ጌታቸር እሸቴ: እርስዎ ለምንድን ነው የማረሚያ ቤቱን ምግብ የማይበሉት?

ዶ/ር ተስፋዬ: ስለማይስማማኝ!

ጌታቸር እሸቴ: የማረሚያ ቤቱ ውሃ የከርሰ ምድር ውሃ መሆኑን ያውቃሉ?

ዶ/ር ተስፋዬ: አላውቅም!

ጌታቸር እሸቴ: የቂሊንጦ ውሃ ደፍርሶ አይተውት አያዉቁም?

ዶ/ር ተስፋዬ: አላውቅም!

( ለግንዛቤ ያህል! የቂሊንጦ ውሃ የከርሰ ምድር ሲሆን አሸዋ ተቀላቅሎ ስለሚመጣ እስረኛው በጨርቅ እያጠለለ ቀድቶ ነው የሚጠቀመው። ከቂሊንጦ ቃጠሎ በሁዋላ ወደ ዝዋይ የተወሰዱ እስረኞች ልብሰቸውን ተቀምተው፣ ባዶ እግራቸውን ባዶ ወለል ላይ ይተኙ ነበር። ለሳምንት ለሁለት ለሁለት ተጣምረው ታስረው ባዶ ወለል ላይ ነበር የሚተኙት። 285 እስረኛ ሁለት ሽንት ቤት ባለው አንድ ቤት ታስሮ የነበር ሲሆን ውሃ ስለሚጠፋ ምግብ የሚባላው እጁን ሳይታጠብ ነበር።)