አትሌት ፈይሳ ሌሊሳ ብራሰልስ በአውሮፓ ህብረት እንደሚገኝ ተገለጸ።
November 1, 2016 Leave a comment
የሪዮ ኦሎምፒክ የብር ሜዳሊያ አሸናፊ የሆነውና በውድድሩ ማጠናቀቂያ ላይ እጆቹን በማጣመር በወገኖቹ ላይ እየተፈጸመ ያለውን ግፍና በደል ለዓለማቀፉ ማህበረሰብ ያጋለጠው ጀግናው አትሌት ፈይሳ ሌሊሳ በሚቀጥለው ሳምንት ብራሰልስ በአውሮፓ ህብረት እንደሚገኝ ተገለጸ።
አክቲቪስት ገረሱ ቱፋ በተለይ ለኢሳት እንደገለጸው አትሌት ፈይሳ በአሜሪካ ስቴት ዲፓርትመንትና በሌሎች መድረኮች ሲያደርግ እንደቆዬው ሁሉ በመጪው ሳምንት ረቡዕ በብራሰልስ አውሮፓ ኅብረት በመገኘት በሀገሩና በወገኖቹ ላይ እየተፈጸመ ስላለው በደል ማብራሪያ ይሰጣል።
ፈይሳ በዚሁ ጉብኝቱ ከአውሮፓ ህብረት ፓርላማ ፕሬዚዳንት ከሚስተር ማርቲን ስቹልዝና ከካቢኔያቸው ጋር የሚገናኝ ሲሆን፤ ረቡዕ ከሰዓት በኋላ ስለ ኢትዮጵያ ጉዳይ በሚሰማበት መድረክ ሀሳቡን ያቀርባል።
በዚህ የኢትዮጵያ ጉዳይ በሚሠማበት ፕሮግራም ላይ እንዲገኙ ፕሮፌሰር መረራ ጉዲናና ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ መጋበዛቸው ታውቋል።
አክቲቪስ ገረሱ ቱፋ እንዳለው የዚያኑ ዕለት ረቡዕ ምሽት በስፍራው ለተገኙት ልዩ የመገናኛና ሃሳብ የመለዋወጫ መድረክ ተሰናድቷል።
በሚቀጥለው ዕለት ሀሙስ እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር ኖቬምበር 10 ቀን ከረፋዱ 11 እስከ 13 ሰዓት ድረስ በህብረቱ ጽህፈት ቤት ፊት ለፊት የተቃውሞ ሰልፍ እንደሚደረግ የገለጸው አክቲቪስት ገረሱ፤ ከአትሌት ፈይሳ ሌሊሳ ጋር በመሆን የወገኖቻቸውን ድምጽ ለዓለማቀፉ ህብረተሰብ ማሰማት የሚሹ በመላው አውሮፓ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ሐሙስ ዕለት ከጧቱ 10 ሰዓት ጀምሮ በብራሰልስ የአውሮፓ ህብረት ጽህፈት ቤት ፊት ለፊት እንዲገኙ ጥሪ አቅርቧል።