ስድስተኛው ፓትርያርክ የሚመረጡበት ጊዜ ይፋ ተደረገ በየካቲት 21

asmerach com
ስድስተኛውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ለማስመረጥ የተቋቋመው አስመራጭ ኮሚቴ ከምርጫው ሂደት ጋርና በተያያዥ ጉዳዮች ላይ ዛሬ ጥር 30 ቀን 2005 ዓ.ም ለጋዜጠኞች በሰጠው መግለጫ የካቲት 21 ቀን 2005 ዓ.ም ምርጫው ተከናውኖ፣ በዚሁ ዕለት ምሽት 12 ሰዓት ላይ፤ ውጤቱ ለሕዝቡ ይፋ እንደሚደረግ አስታውቋል፡፡

መራጮች ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት፣ ከጥንታውያን ገዳማትና አድባራት፤ ከካህናት፤ ከምእመናን፤ ከሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶችና ከማኅበረ ቅዱሳን አባላት የተወከሉ ሲሆኑ ጠቅላላ ቁጥራቸው 800 መሆኑን ያስታወቀው መግለጫው፡- በመጨረሻ እጩ ሆነው የሚቀርቡ አምስት እጩ ፓትርያርኮች የካቲት 18 ቀን 2005 ዓ.ም ለሕዝብ ይፋ እንደሚደረጉ አመልክቷል፡፡ የምርጫውን ሂደት ለማስፈጸም የወጣው መግለጫ “ምእመናን ካህናትና የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ከአጥቢያ ቤተ ክርስቲያናቸው ማንነታቸውን የሚገልጽ ደብዳቤ በመያዝ ለእጩነት የሚያስቡትን አባት አስመራጭ ኮሚቴው ጽ/ቤት ድረስ በአካል በመቅረብ እንዲሁም ከሀገር ውጪ የሚገኙ በፋክስ ቁጥር 0111567711 እና 0111580540 ከየካቲት 1 እስከ 8 ቀን 2005 ዓ.ም እንዲጠቁሙ” ጥሪውን አቅርቧል፡፡

ስድስተኛ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ በመሆን የሚመረጡት አባት እሑድ የካቲት 24 ቀን 2005 ዓ.ም በዓለ ሢመቱ በቅድስት ሥላሴ ካቴድራል እንደሚፈጸም መግለጫው አመልክቷል፡፡

ከየሀገረ ስብከቱ በመራጭነት የተወከሉ ሰዎች የካቲት 19 ቀን 2005 ዓ.ም አዲስ አበባ እንዲገቡ ያዘዘው የአስመራጭ ኮሚቴው መግለጫ እግዚአብሔር አምላካችን የወደደውንና የፈቀደውን በመንበሩ ያስቀምጥ ዘንድ ካህናትና ምእመናን ከየካቲት 1 እስከ 8 ቀን ድረስ አምላካቸውን በጸሎት እንዲጠይቁ ለአንድ ሱባኤ የሚቆይ የጸሎት ጊዜ መታወጁን አስታውቋል፡፡

eotc-mkidusan.org

posted by Aseged Tamene

About Aseged Tamene
Your rights are your security. When you, 'give up your rights for security", it's not security you get, but slavery.'

Leave a comment