ትራምፕ 3ኛው የዓለም ጦርነት የሚጀመረው በሄላሪ ነው አሉ

   – የምርጫ ውጤትን እቅጩን የሚገምቱት ፕሮፌሰር፣ ትራምፕ ያሸንፋል ብለዋል
– ሪፐብሊካኑ ኮሊን ፖል ድምጻቸውን የሚሰጡት ለዲሞክራቷ ሄላሪ እንደሆነ አስታውቀዋል

የሳምንታት ጊዜ በቀረው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ሪፐብሊካኑን ወክለው የሚወዳደሩት አነጋጋሪው ዕጩ ዶናልድ ትራምፕ፣ 3ኛው የዓለም ጦርነት የሚጀመረው ተፎካካሪያቸው ሄላሪ ክሊንተን ይዛው በተነሳቺው የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ሳቢያ ነው ሲሉ ተናገሩ፡፡
ሄላሪ ክሊንተን በሶርያ ጉዳይ ላይ የያዘቺው እቅድ በአሜሪካና በሩስያ መካከል የከፋ ግጭት የሚያስከትልና ለሶስተኛው የዓለም ጦርነት መነሻ ሊሆን አንደሚችል ትራምፕ ባለፈው ማክሰኞ ባደረጉት ቃለ ምልልስ ማስጠንቀቃቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
የሄላሪን ዕቅድ በመደገፍ በምርጫው ድምጻችንን የምንሰጣት ከሆነ፣ ሶስተኛው የዓለም ጦርነት መጀመሩ አይቀሬ ነው ያሉት ትራምፕ፤ ሄላሪ ስታብጠለጥለው ከከረመቺው ከሩስያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን ጋር ለመደራደር ያላት ብቃት እንደሚያጠራጥራቸው በመግለጽ፣ በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን ግንኙነት ታበላሸዋለች ብለዋል፡፡
ያልተለመዱ ክስተቶች የተስተናገዱበት የዘንድሮው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ቅስቀሳ እየተጧጧፈ ወደ መጨረሻው ምዕራፍ በደረሰበት በአሁኑ ወቅት፣ ሪፐብሊካኑ የቀድሞው የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኮሊን ፖል ዲሞክራቷን ሄላሪን እንደሚመርጡ ማስታወቃቸውን የዘገበው ደግሞ ስካይ ኒውስ ነው፡፡ ሊዲሞክራቷ ዕጩ ድምጻቸውን እንደሚሰጡ በይፋ የሚናገሩ ስመጥር ሪፐብሊካኖች እየተበራከቱ መምጣታቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ኮሊን ፖልም ሄላሪ እንደ አገር መሪ ያላትን የካበተ ልምድና ክህሎት በማድነቅ ድምጻቸውን ለእሷ እንደሚሰጡ ባለፈው ማክሰኞ ማስታወቃቸውን ገልጧል፡፡
በተያያዘ ዜና ምንም እንኳን በርካታ ቅድመ ትንበያዎች በቀጣዩ ምርጫ ዲሞክራቷ ሄላሪ በለስ እንደሚቀናት እያመላከቱ ቢሆንም፣ የአሜሪካን ምርጫ ውጤት በመተንበይ የሚታወቁት የፖለቲካ ተንታኙ ፕሮፌሰር ሄልሙት ኖርፖዝ ግን፣ በስተመጨረሻ ድል የትራምፕ ትሆናለች ሲሉ መተንበያቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
ላለፉት 100 ያህል አመታት በአሜሪካ ከተከናወኑ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫዎች ከአንዱ በቀር የሁሉንም ውጤት በትክክል የገመቱት የኒውዮርኩ ሰኒ ስቶኒ ብሩክ ዩኒቨርሲቲ መምህር ፕሮፌሰር ሄልሙት ኖርፖዝ፣ በቀጣዩ ምርጫ ትራምፕ እንደሚያሸንፉ በይፋ ተንብየዋል፡፡
ፕሮፌሰር ኖርፖዝ የፈጠሩትና ያለፈውንና የወደፊቱን የፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ውጤት የሚያመላክተው የትንበያ ቀመር፣ እ.ኤ.አ ከ1912 አንስቶ በተደረጉት የአገሪቱ ምርጫዎች ላይ ያቀረበው ትንበያ ከአንዱ በስተቀር በሁሉም ስኬታማ እንደነበር የጠቆመው ዘገባው፣ ቀመራቸውን ተጠቅመው የሰጡት ትንበያ ያልያዘላቸው እ.ኤ.አ በ2000 በተካሄደው ምርጫ ብቻ እንደነበርም አስታውሷል፡፡

About Aseged Tamene
Your rights are your security. When you, 'give up your rights for security", it's not security you get, but slavery.'

Leave a comment