ዛሬ ማለዳ በአዲስ አበባ ቴዎድሮስ አደባባይ አካባቢ በደረሰ የመኪና አደጋ የ4 ሰዎች ህይወት አለፈ ተባለ…

ሰባት ሰዎች በህይወት ተርፈው ወደ አቤት ሆስፒታል ለህክምና ተወስደዋል ተብሏል፡፡

ሸገር ከእሣትና ድንገተኛ አደጋዎች መከላከያና መቆጣጠሪያ ባለሥልጣን የህዝብ ግንኙነት ባለሙያ አቶ ንጋቱ ማሞ እንደሰማው ሚኒባስ ታክሲው ከፒያሳ ወደ ጥቁር አንበሳ ቁልቁል እየወረደ እንዳለ ቴዎድሮስ አደባባይ ሲደርስ መንገዱን ለቅቆ ለግንባታ የተቆፈረ ቦታን ጥሶ ገብቷል፡፡

አደጋው ማለዳ 1 ሰዓት ከ40 ደቂቃ ገደማ መከሰቱንም ሸገር በአካባቢው ከነበሩ መንገደኞች ሰምቷል፡፡

አቶ ንጋቱ እስከ ረፋድ 3 ሰዓት ድረስ ተሽከርካሪው ከገባበት ወንዝ ውሰጥ ስድስት ሰዎችን በህይወት እና የሁለት ሰዎችን አስክሬን ማውጣት መቻላቸውን ነግረውን ነበር፡፡ ከቆይታ በኋላ አቶ ንጋቱን ጠይቀን እንደሰማነው በተሽከርካሪ ውስጥ የነበሩ የ4 ሰዎች (የ3 ሴትና የ1 ወንድ) አስክሬን ማውጣት ተችሏል፡፡

7 ሰዎችንም በህይወት ማትረፍ ተችሎ ወደ አቤት ሆስፒታል ለህክምና ተልኳል ብለዋል፡፡

መኪናው ቁልቁል እየተንደረደረ ባለበት ሰዓት ረዳቱና አንዲት ሴት ተሳፋሪ በር ከፍተው ዘለዋል፡፡ በህይወትም ለመትረፍ ችለዋል ሲሉ አቶ ንጋቱ ነግረውናል፡፡

አሽከርካሪው ቁልቁለቱን መውረድ ሲጀምር “ፍሬን እምቢ ብሎኛል እየዘለላችሁ ራሳችሁን አድኑ…” እያለ ሲጮህ እንደነበረ ከረዳቱ ሰምተናል፡፡ ግን ወደ ወንዙ ከመግባቱ በፊት ለመዘለል የደፈሩት ረዳቱና አንዲት ሴት ብቻ ናቸው ብለዋል፡፡

በእነሱም ላይ ጉዳት መድረሱን አቶ ንጋቱ ነግረውናል፡፡ ሾፌሩ በህይወት ተርፎ ወደ አቤት ሆስፒታል ተወስዷልም ብለዋል፡፡

የኦሮሚያ ሰሌዳ የለጠፈው ሚኒባስ ታክሲ የአደባባዩን ጠርዝ አጋጭቼ አቆማለሁ በሚል ተሽከርካሪውን ቁልቁል እንደነዳውና አጥሩን ጥሶ አልፎ ከ5 ሜትር በላይ ርቀት ካለው ወንዝ ውስጥ እንደገባም ነግረውናል፡፡

በተደጋጋሚ የተቆፈሩ ጉድጓዶች ባለመደፈናቸው አደጋ ይከሰታል ያሉት አቶ ንጋቱ በዛሬው አደጋም ሰዎቹ የሞቱት እና የተጐዱት ተከፍቶ ከተተወው የጥልቁ ወንዝ ውስጥ በመግባታቸው ነው ብለዋል፡፡

በታክሲው ውስጥ 13 ሰዎች መኖራቸውን አረጋግጠናል የሞቱትን 4 ሰዎች አስክሬንና የተጐዱትን ማውጣት ችለናል ያሉት አቶ ንጋቱ “ግን መኪናው ቁልቁል ሲወርድ ይዞ የገባው ሌላ እግረኛ ካለ አሊያም አካባቢው ላይ የጐዳና ተዳዳሪዎች ስለሚተኙ እነሱን ይዞ ገብቶ ይሆናል የሚል ጥርጣሬ ስላለን ፍለጋውን ባለሙያዎቻችን ቀጥለዋል” ብለዋል፡፡

aseged tamene image

About Aseged Tamene
Your rights are your security. When you, 'give up your rights for security", it's not security you get, but slavery.'

Leave a comment