በደቡብ ኢትዮጵያ ኮንሶ ልዩ ወረዳ ውጥረቱ እንደነገሠ ነው።

በህወሓት(ደኢህዴን) እና የእነሱ ቅጥረኛ በሆኑት የአካባቢው ሆድ አደር ተሿሚዎች ምክንያት የማንነት እና ዘር የማጥፋት አደጋዎች ከፊታችን ተደቅኖብናል፤ ከዚህ በፊትም በስውር ሲፈፀምብን ነበር ይላል አንድ የኮንሶ ወጣት በውስጥ መስመር በላከልኝ መልዕክት።

የኮንሶ ልዩ ወረዳ በደቡብ ኢትዩጵያ ውስጥ ከሚገኙት 8 ልዩ ወረዳዎች አንዷ ናት ። በማዕከላዊ እስታቲስቲክስ ዳታ መሰረት ወደ 305,000(ሶስት መቶ አምስት ሺ) የሚያክል ህዝብ ብዛት አላት። ይህንን የሚያክል ህዝብ ይዛ ቀድሞንም ኢ-ፍትሃዊ በሆነ መንገድ በወረዳ ደረጃ በመዋቀሯ ምክንያት የአካባቢው ህዝብ የመንግስት አገልግሎት ሰጪ ተቋማት በአቅራቢያው ባለማግኘት ምክንያት ምን ያክል በከፋ ስቃይ ውስጥ እንደነበር መገመት አያዳግትም። በነገራችን ላይ እንደ አጠቃላይ ከተመለከትን የደቡብ ኢትዩጵያ ህዝቦች በኢትዮጵያ ውስጥ ካሉት ሁሉም ክልሎች ሲነጻጸር በመሰረተ ልማት ዝርጋታና በእድገት የመጨረሻ ደረጃ ላይ እንደሆነ ወርልድ ባንክን ጨምሮ ሌሎች የአለም አቀፍ ድርጅቶች ከአንድ አመት በፊት ሪፖርት ማውጣታቸውን አስተውሳለሁ ። ከዚህ አንፃር ስንመለከት በኮንሶም ይሁን ሌሎች የደቡባዊ ኢትዩጵያ ወረዳዎች እና ዞኖች አንድ ገበሬ የመንግስት አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ለማግኘት በአማካይ የ5 ወይንም የ6 ሰዓት መንገድ በባዶ እግሩ መጓዝ ይጠበቅበታል። ደርሶ መልስ ባላጋንን የ11 ሰዓት መንገድ። ለዛውም በየአካባቢው በወያኔ መስፈርት የተሾሙት ትንንሽ መሳፍንቶችን ግልምጫ እና ስድብ ለማስተናገድ። ወደ ኮንሶ ጉዳይ ስንመጣ የኮንሶ ህዝብ የፍትሕ ያለህ የሚል ጩሄት ለክልልና ፌደራል መንግስታት ማስተጋባት የጀመሩት ከዛሬ 8 ወር በፊት ነው። እርግጠኛ ነኝ የልማት እና ተያያዥነት ያላቸውን ጥያቄዎች ማቅረብ የጀመሩት በዚህች ስምንት ወር ብቻ ሳይሆን ከዛ በፊትም በነበሩበት ተከታታይ ጊዜያት ይሆናል የሚል እምነት አለኝ። አሁን በዚህ 8 ወራት ውስጥ እያየለ የመጣው የኮንሶ ህዝብ ጥያቄዎች በአይነቱም በይዘቱም ጠንከር ያሉ ናቸዉ ። ሁለት መሰረታዊ ጉዳዩች ጋር የተገናኘ ነው ይላል ከአካባቢው መረጃ የሰጠኝ ግለሰብ። አንደኛው ወቅቱን በትክክል ባያስታውስም ከቅርብ ጊዜ በፊት በአንድ የአለም አቀፍ ድርጅት አማካኝነት በኮንሶ አከባቢ በተደረገው ጥናት መሰረት በአካባቢው ከፍተኛ የማዕድን ክምችት እንደተገኘና እስከ አሁን ጉዳዩ በምስጢር ተይዞ ተቀምጧል ይላል ወጣቱ። ከዚህው ጋር በተያያዘ ለቁፋሮ ቅድመ ሁኔታዎችን ለማመቻቸት የክልሉ መንግሥት እና የአካባቢው ተሿሚ መሳፍንቶች በርካታ የኮንሶ ነዋሪዎችን በማስገደድ ከነበሩት ቦታ ከታላመዱበት የአኗኗር ዘይቤና ባህል በማፈናቀል ወደ ባስኬቶ ልዩ ወረዳ እና ወደ ደቡብ ኦሞ ዞን በሰፈራ ፕሮግራም በግዳጅ ማንነታቸዉ በማስካድ እየወሰዷቸው ነው። ከዚህ በፊትም በግዳጅ ብዙ ሰው ተፈናቅሎ በሰፈራ ፕሮግራም ሄዷል ይላል ወጣቱ ።ሌላው በቅርቡ የተመሰረተ አንድ ሰገን ዞን የሚባል የኮንሶ ልዩ ወረዳ አጎራባች አለ ። ደቡብ ክልል ውስጥ 13 ነባር ዞኖች እና 8 ልዩ ወረዳዎች አሉ። ይህኛው 14ኛ መሆኑ ነው። የሰገን ዞን ሲመሰረት ከዚህ ቀደም በኮንሶ ወረዳ ክልል ውስጥ የነበሩ በርካታ ቀበሌዎች በግዳጅ ወደ ሰገን ዞን እንዲካለሉ ተደርጓል ይላል። በዚህም ምክንያት የኮንሶ ማንነት በኃይል በማስካድ ያልታወቀ በቅርቡ በመጣ ሰገናዊ ማንነት በኃይል የማጥመቅ ስራ እየተሰራ ይገኛል። ሌላኛውና ሁለተኛው አንኳር ጥያቄዎቸው 305,000 ህዝብ ሆነን ሳለ በአንድ ወረዳ መስተዳድር ስር መዋቀራችን ተገቢ አይደለም ቀድሞንም በዞን ደረጃ መሆን ነበረበት ሰለዚህ መንግሥት ያለውን የህዝብ ቁጥር ታሳቢ በማድረግ የዞን ማዋቅር ሊሰጠን ይገባል የሚል ጥያቄ ነው። በተጨማሪም ኋላ ቀር ነን መንገድ እና የመሳሰሉ የልማት ስራዎች እንዲሰራልን የሚሉ ጥያቄዎችም አሉበት ። እነዚህንና የመሳሰሉትን ጥያቄዎች አንግበው የኮንሶ ህዝብ ሰላማዊት ህዝባዊ ትግል ከጀመሩ ይህ 8ኛው ወራቸው ነው ። ከ4 ጊዜ በላይ የአካባቢው ተወካዮች ወደ ክልልና ፌደራል መንግሥት ተንቀሳቅሰዋል። የተሰጣቸው ምላሽ ግን ያልጠበቁት ሆኖ ነው ያገኙት። የክልሉን ልዩ ኃይል፣ የፌደራል ፖሊስ ፣በደቡብ ክልል የፀጥታ ኃይል ዩኒፎርም ጭንብል አጋኣዚ እና የመሳሰሉትን ታጣቂዎች በአካባቢው ማራገፍ ነው የሆነው። እስከ አሁን ድረስ ብዙ ሰዎች በጥይት ተደብድበው ተግድለዋል ብዙ ሰውም ታስሯል። የአካባቢው ባህላዊ ንጉስ ሳይቀር በአሁኑ ሰዓት እስር ላይ ናቸዉ ።በዛሬው እለትም አንድ ታወቂ ነጋዴ ታፍኖ እንደተወሰደ ከስፍራው መረጃ ወጥቷል። ትግሉ ግን አልቆመም የሚቆምም አይነት አይደለም። እጅግ በጣም የሚያሳዝነው ነገር ይላል ወጣቱ በአሁኑ ሰዓት የኮንሶን ህዝብ መንገድ በመምራት እና ልዩ ልዩ እርዳታ በማድረግ እያሰጨፈጨፉና እያሰቃዩ የሚገኙት ከኮንሶ አብራክ የወጡ የአካባቢው ተሿሚዎች መሆናቸው ነው በማለት ቋጭቷል። በኔ እይታ ከኮንሶ አብራክ የተውጣጡ ተሿሚዎች በመተግበር ላይ የሚገኙት ጭካኔ የተሞላበት ድርጊት በአሁን ሰዓት ለአካባቢዬና ለህዝቤ ነፃነት እታገላለሁ ለሚሉት እና ለተከታዮቻቸው በተጨማሪም ከእርሱም ፍጹም ነፃነት በመሻት ላይ ላሉ ሁሉ ትልቅ መልእክት እያስተላለፈ ይገኛል።ነፃነት ማለት በየቦታው ትናንሽ መንግስታትን በአንድም በሌላ መልኩ እየተደራጁ በመፍጠር መካከለኛውንና የበታችኛውን የህብረተሰብ ክፍል ወደ ታች ደፍጥጦ በመያዝ መዝረፍ እና ደም ዕምባ ማስለቀስ እንዳልሆነ ያመላክታል።

About Aseged Tamene
Your rights are your security. When you, 'give up your rights for security", it's not security you get, but slavery.'

One Response to በደቡብ ኢትዮጵያ ኮንሶ ልዩ ወረዳ ውጥረቱ እንደነገሠ ነው።

  1. yohannes says:

    ከዚህ መሃይም መንግስት ጋር አንቀጥልም

    Like

Leave a comment